Sunday, May 1, 2016

ፍቅርን በኢትዮጲያንኛ ጉራማይሌ፥ (Love in Ethiopian pidgin)



ፍቅርን በኢትዮጲያንኛ ጉራማይሌ፥ (Love in Ethiopian pidgin)

       ፍቅርን በማወቅ፣ ፍቅርን በመከወን የሚያህለው የለም ከሚባል አገር የሆነ ፈረንሳዊ የዛሬ ስንትና ስንት ዓመት Readers Digest በተባለ መጽሔት እንዳነበብኩት ኦፔራ ሊያይ ገብቶ በኦፔራ ዘማሪዋ ድምፅ ብቻ ሳይሆን በውበትዋም ይነኾልላል፣ ብሎም ይሻፍዳል።

    እናም ከእቅፍ አበባ ጋር ፖስት ካርድ ላይ እንዲህ ብሎ ጻፈና ላከላት።

         "When one sees you, one loves you. When one loves you, where does one see you?"

   ያየሽ ይወድሻል፤ የወደድሽ ዌት አግኝቶ ሊቀመጭልሽ ይችላል? "ሊቀመጭልሽ" በፈረንጅኛው ላይ የለም፤ ሆኖም እንኳን ፈረንሳይ በቁጥብነቱ የሚታወቅ፣ ጿሚ ጸሎተኛ፣ ቤተስኪያን ሳሚ የሆነ እንኳ ያችን የመሰለች ልጅ ቤቱ ጋብዞ የሳሎን ጌጥ ሊያደርጋት ወይም የፊደል ሰራዊት ሊያስቆጥራት ነው ተብሎ እንደማይታሰብ እሙን ነው። ፍቅርን ለመከሸን (consummate እንዲል ፈረንጅ) ወይም ለመወዛዛት ጥናት፣ ፊደል ማስቆጠር እንዴት ያለ መላ እንደሆነ ደበበ ሰይፉ በብርሃን ፍቅር ቅጽ 1 መድብሉ 'ያች ቆንጂት'በተባለ ግጥሙ ፍንትው አድርጎ ሲያሳይ፥

   "--ፊደሏን በጅዋ ጨብጣ
         (ዐይነ ጥላ ነበረባት
          ትምህርት እሚከለክላት)
          "አታስተምረኝም?" ትለኛለች
          ያይኔን ብርሃን እየሞቀች
         "እሺ ቆንጂትዬ"እላታለሁ
          መጻሕፍቴን እየገፋሁ።

         አጠገቤ ትቆማለች
                   ቆንጂትዬ
        ስንጥሯን እንደ ጠቆመች
        ጣቴን ያዝን እያለች
        ይዛትና
        ጠጋ አድርጌ አቅፋትና
        --በይ ስላት
        --በይ ስላት
              እቆይና
       '' ጠንቁላ '' ስትለኝ
              አያትና
        ድምፅዋ ሲደክም እሰማና፤
       "ምነው ቆንጂትዬ?"
       "ምንም አይደል ጋሽዬ"

        ብር ብላ ትሔዳለች
                    ቆንጂትዬ
        እንደገና ልትመጣ፤
       (አፍታ ሳትቆይ
        ነጠላዋን ቆንጥጣ)
       "እንደ እማዬ አታለብሰኝም?" ትለኛለች
        ያይኔን ብርሃን እየሞቀች
       'ነይ ላልብስሽ'እላታለሁ
        መጻሕፍቴን እየገፋሁ።
        አለብሳት ስል አይስማማት
        አንዴ ሲያጥር ሲረዝምባት
        ግራ ገባኝ
        ግራ ገባት።
        ፈርዶብኝ
        ፈርዶባት።      

       ብር ብላ ሔደች ቆንጂት
        በማግሥቱ እኅቴ ናት
       ነጠላዋን የሰጠቻት።"

    ወደ ፈረንሳይ ፍቅርን ያውቃል ስለመባሉ ነገር ስንመለስ በግድ ሳይሆን በፍቅር፣ እንዲሁም ሜሪ አርምዴ በዘመኑ መንፈስ ተቀባይነት በነበረው "ጫማው ጥልፍልፍ ኮፍያው ገዳዳ/ መጣ ጦር ሰራዊት በግድ የሚበዳ!"ብላ የዘፈነችውን ማህበረሰቡ ለዘላለሙ ከምር በመውሰድ ኢትዮጲያዊው ወንድ ሴትን ልጅ እንደ እቃ እንዳይወስድ፤ ኢትዮጲያዊዋ ሴትም ራሷን እንደ እቃ መገልገያ አድርጋ እንዳትቆጥር፤ ብሎም ጣፊጦዋን ወንዱን በማነሁለል አንዳች ግብ የምትመታበት መሳሪያ ብቻ አድርጋ እንዳትወስደው፤ ይልቁንም ፍቅርን ሰጥቶ በመቀበል፣ በመቀባበል ሰውነትን ከፍ የሚያደርግ እጹብ ድንቅ ደስታ እንደሚገኝ ለማስረዳት ነው መሰለኝ በፈረንሳይ አገር ወይም በፈረንሳይኛ የተማሩት የቀድሞው የዝነኛው የክብር ዘበኛ ባልደረባ ሻምበል አፈወርቅ ዮሐንስ "የማፍቀር ጥበብ" የሚል መጽሐፍ አሳትመው እንደነበር አስታውሳለሁ።

    መጽሐፉን እንዴት እና ከዬት እንዳገኘሁት አላስታውስም፤ ብቻ በልጅነታችን "አዋቂዎች" እንዳናነብ ከምንከለከላቸው "እውነተኛ ታሪክ"ተብሎ እንደተጻፈው የአቶ ሃይለስላሴ ደስታ የውሸት "የሚያቃጥል ፍቅር" ደስ የሚል የባለጌ ነገር ይኖርበት ይሆናል ብዬ ተሰርቄ ባገላብጠውም ሻምበሉ ከቆፍጣና ወታደርነታቸው በተጨማሪ ተራማጅነትን ከወግ አጥባቂነት ጋር ያዛመዱ የፈረንሳይ ተማሪ ኢትዮጲያዊ እንደሆኑ ነው የተገለጠልኝ (ይሄ የተገለጠልኝ አሁን ነው) እና እሱ እንደተገለጠልኝ የሻምበል አፈወርቅን "የማፍቀር ጥበብ" እንደ አቶ ሃይለስላሴ "የሚያቃጥል ፍቅር" ማገላበጥ አቃተኝ።

       ስለፍቅር ሳወራ እንደ በዛብህና እንደ ሰብለ እስከ መቃብር ስለሚወስደው ፍቅር አይደለም የማወራው፤ በሰማንያ (ግን ሰማንያ ለምን ተባለ በሞቴ?)ታስሮ Until death us do part የሚባለውን ብቻም አይደለም ፍቅር ብዬ የማስበው። ለእኔ ተያይቶ፣ ተከጃጅሎ በቅጽበት ወስኖ ለመወዛዛት ጥግ መሻት በራሱ ፍቅር ነው! ዘላቂ መሆን አለመሆኑ፣ በማዘጋጃ ቤት መዝገብ መግባት አለመግባቱ፣ ተክሊል ማስደፋት አለማስደፋቱ ወይም በኒካሃ ማስቀፍደድ አለማስቀፍደዱ ለእኔ እምብዛም ቁምነገር አይደለም። ትልቁ ቁምነገር ምንም ሳይተዋወቁ ገና እንደተያዩ ከአያት ቅድመ አያታቸው በወረሱት እንደ ዘረኝነት ባለ ጅል ታሪክ በጥላቻ መንፈስ ለመተራረድ፣ ደም ለመቃባት ከመፈላለግ ይልቅ መግነጢሳዊ በሆነ መሳሳብ ተወዛዝተው ለመደሰት መፈለጋቸው ነው።

      ስለተክሊል፣ ስለሰማንያ ሲነሳ አንዱ ጨዋ ፈረንጅ ደግሞ "The girl I marry would be an aristocrat in the living room, an economist in the kitchen, and a harlot in bed." ብሎ ሶስት መስፈርት ያወጣና ይህንኑ ታሟላላች ብሎ ያሰባትን ያገባል። መስፈርቱን የምታሟላው ሴትዮ ግን በሚያሰቅቅ ሁኔታ ቅደም ተከተሉን አፋልሳለች። ሳሎን ላይ ሽርሙጥሙጥ እያለች ከተጋበዙት እንግዶች ጋር ሁሉ እየተዳራች ሰውዬውን በቅናት እንዲከንፍ አደረገችው፤ ማጀቱ ላይ እንደ አሪስቶክራት ስትንቀባረር ወጡ አረረ፤ መኝታ ቤት አልጋ ላይ አላስቀምስህ ብላ ደርሳ ኢኮኖሚስት ሆነች። ባልዬው ምን ማድረግ ይችላል በዚህ ሁኔታ ያው American Beauty በሚል ርዕስ በሚታየው ፊልም ላይ ሚስቱ ለሌላ እየሰጠች ለሱ የከለከለችው ባል (Kevin Spacey ነው መሪ ተዋናዩ) እሷን ጎኑ አጋድሞ ሴጋ እንደሚመታው ከመምታት በቀር! "በአምሳ በሰላሳ ሲገዛ ፈረስ/ስናዳድ አደርኩኝ ገዝቼ የሰው አጋሰስ" እንዳይል እንደ አሰፋ አባተ እንኳን አሜሪካዊው እኔም ሙሉ ለሙሉ ያስታወስኩት አይመሰለኝም። የፍተወት ፍሙ ምሱን ያገኝ ዘንድም እንደ ድሮው ሰርቶ አደሩ ሴትኛ አዳሪ ጋር በቀላሉ ሄዶ ሊያባርደው አይችልም፤ ዋጋው እሳት ስለሆነ በሌላ ፍም ተለብልቦ ይመጣል፤  ከዚህ ይሰውራችሁ!

   ከሴቶች በኩል ግን (የፈረንጆቹን ማለቴ ነው) ሊያገቡት የሚያስቡት ወንድ ምን ምን መስፈርት ማሟላት እንዳለበት ሊስት አውጥተው እንደሆነ አልሰማሁም።ይልቅ የኛዎቹ በደርግ ጊዜ ሊያገቡት ያሰቡት ወንድ ሶስት "" ዎችን ማለትም ቮልቮ፣ ቪላ እና ቪዲዮ ያለው መሆን አለበት ብለዋል ሲባል ሰምቼያለሁ። አሁን ይሄንን አንድሳይሽረው አልቀረም። የአሜሪካ ቪዛ ያለው ማንም ጉፋያ ብርጭቆ የመሰለች ልጅ አሜሪካ ከመድረሷ/ከማድረሱ በፊት እስከቢቃው ሊቀመጭል ይችላል፤ እዚህ ከመጣች በኋላ ስላለው ነገር ግን It would be at his own risk.

      ፍቅር፣ መወዛዛት ደስታ ነው፤ መዘዝም ቢኖረው ላወቀበት ደስታው ስለሚያመዝን አሜሪካ የነፃነት አዋጅ በሚለው ታሪካዊ ሰነዱ ከሕይወትና ከነፃነት ጋራ "ደስታንም ማሳደድ (The Pursuit of Happiness)" ለወንዶች ብቻ ሳይሆን ለሴቶቹም እውነት መሆኑን የተገነዘቡ አንዲት የሰባ አምስት ዓመት ባልቴት የዛሬ ስንትና ስንት ዓመት ባነበብኩት Newsweek ወይም Time መጽሔት ላይ "ለምሳሌ እኔ ትናንትና ማታ ወሲብ አድርጌያለሁ (For instance, I had sex last night.) ካሉ በኋላ ባል የሞተባቸውን የእድሜ ባለጸጋ እኩዮቻቸውን ሲያበረታቱ "ስላረጀሽ ወይም ባል ስለሞተብሽ ብቻ ሕይወትን መኖር አታቁሚ፤ ከወንዶች እኩዮቻችን ተምረን በገንዘባችን እኛም ሳናፍር ሳንሳቀቅ ወጣት ጎረምሶችን ገዝተን አለማችንን ማየት እንችላለን ሲሉ ቶማስ ጀፈርሰን ዋና መሃንዲስ በሆነበት "የነፃነት አዋጅ" መሰረት ደስታን ማሳደድ ወይም መሻት ምን እንደሆነ በማሳየት አዲስ dimension ወይም ልዩ perspective አስጨብጠዋል።

     በነገራችን ላይ እንዲህ ያሉ የፈረንጅ ባልቴቶች በገንዘባቸው ጎረምሶችን እየገዙ በግላጭ ፍስሃ ከሚያደርጉባቸው አገሮች አንዷ ጋምቢያ የምትባለው የምዕራብ አፍሪቃ አገር ስለመሆኗ .. 2011 እዚያ በተገኘሁበት ጊዜ በዓይኔ በብረቱ ለማየት ችያለሁ። በሌላ አነጋገር በባንጁል የጋምቢያ ዋና ከተማ ከሴት አዳሪ በተጨማሪ በይፋ የወንድ አዳሪ አለ! ወፌፌው አምባገነናቸው ያህያ ጃሜ ሻሪያ ከደነገገ በኋላ ይህን ደስታን የመሻት መብት አናቅፎት እንደሆነ አላውቅም፤ አላህ ያናቅፈውና!

     የአሜሪካኖች ደስታን የመሻት የነፃነት ስሜት ግን ግራ ያጋባል። በአንድ በኩል ደስታን በመሻት መብት ወሲብን በቀላሉ እና በቅርብ ሊያገኙት ሲችሉ አንዳንድ መብት ማለትም የሴት መብት አለቅጥ የተለጠጠ በመምሰሉ፣ በዚህም የተነሳ በውሃ ቀጠነ ሴቷ ተነስታ በወሲብ ማዋከብ ክስ ወንዱን ለዘብጥያ ልትዳርገው ስለምትችል ወንዱ ቢከጅልም፣ እንዲሁም ሴቷም ከሱ እኩል የከጀለች ቢመስለውም እጅግ ጥንቃቄ፣ ማክበር፣ መከባበር ሲያበዛ፣ ሲያበዙ እየተከጃጀሉ ሞሜንተሙ (momentum) ያመልጣቸዋል።

እናም "ልብ ሲፈቅድ መግደርደር ራስን መግደል" የተባለው ይደርስባቸዋል፤ ተረት ብቻም አይደለም፤ በብድ እጦት፣ በፍቅር አለመርካት (unrequited love) ሳቢያ ድብርት እንደ መርግ ሲጫናቸው ራሳቸውን የሚገሉት ቁጥር ቀላል እንዳልሆነ ነው ዜናቸው፣ አሃዛቸው የሚያሳየው።

    ከዚህም የባሰ አለ! በቅርቡ ትዳሬን (ኑሮዬን) ልደጉም ቀለል ባለ ስራ ተጨማሪ ፍራንክ የሚለቃቀምበትን ስሻ የተለያየ ነገር ከመደብር፣ ግሮሰሪ፣ መድሃኒት ቤት ወዘተ ተገዝቶ በራፋቸው ድረስ እንዲመጣላቸው ለሚፈልጉ በመኪና ማቅረብ አንዱ በመሆኑ ይህንኑ የሚያሳልጠውን ድርጅት ተጠጋሁትና ስለ ስራው ቅኝት (orientation) ወሰድኩ። እናም ከአልኮሆል መጠጥ በቀር ማንኛውም ነገር ሲጋራንም ጨምሮ ደንበኞች በር ድረስ ሊወሰድላቸው እንደሚችል፤ ሆኖም ሲጋራውን ትዕዛዙ የመጣበት ቤት ከማስረከባችን በፊት በር ላይ የሚረከበን ሰው ከአስራ ስምንት ዓመት በታች ከመሰለን ትልቅ ሰው እንዲጠራልንና እንድናስረክብ ወይም የራሱን እድሜ የሚያስረዳ መታወቂያ እንዲያሳየን እንድንጠይቅ መመሪያ ተሰጠን። ይህ ይህን ስራ በሚያሳልጠው ድርጅት መመሪያ ላይ በጽሑፍም ሰፍሯል፤ ያልሰፈረው በውስጠ ታዋቂ ግን የሚታወቀውን እኔንና እንደኔው በትርፍ ጊዜዋ ይህን ስራ ለመስራት የመጣችውን አፍሪካዊ አሜሪካዊን እንድታሰለጥን የተመደበችው ነጭ አሜሪካዊ "አንዳንድ ደንበኞች ማናፈሻ (ventilator) ተገዝቶ እንዲቀርብላቸው ይጠይቁ ይሆናል፤ በቴክሳስ ግዛት ይህን ከማድረግ የሚገታ ሕግ ስለሌለ ምን መገረም ቢያድርብን መገረማችንን በሆዳችን አድርገን ማናፈሻ ወይም ማባረጃውን ገዝተን ማስረከብ ነው ስትል በተለይ እኔን በቆረጣ እያየች "ባይልለት ነው እንጂ የሁሴን አህመድ ልጅ እንኳን ቬንቲሌተር በማቅረብ ይህን ሃራም ሊሰራ በድፍን አለም ያሉ ሴቶችን ሁሉ ከፀጉር እስከ እግር ጥፍራቸው ድረስ በድንኳን ታጅለው እንዲዞሩ የሚያደርግ ነበር" በሚመስል መንፈስ መልዕክቷን በዘዴ አስተላለፈች፤ ለእኔ!

         አለመተዋወቅ! ብንተዋወቅ ግን በዮሐንስ አድማሱ "ሰይጣን ሰለጠነ" ግጥም ውስጥ እንዳለው ከእሷና In God We Trust እያለ ከሚቆነነው ማህበረሰቧ "አለመጠን የባስኩ ክርስቲያን" መሆኔን ተረድታ ትንፋሿን ከማባከን ትቆጠብ ነበር። የሆኖ ሆኖ የአሜሪካን ሴቶች የፍተወት ፍማቸውን እንዲያባርድላቸው የሚጠቀሙበት ይህ መሳሪያ "ደስታን በመሻት መብት" ውስጥ ይበልጥ ተቃርኖ ያየሁበት ስለመሰለኝ ወደ መናኛ ምርምርም ወሰደኝ። እንኳን አሜሪካዊው ወንድ ከየአገሩ ወደ አሜሪካ የሚጎርፈው ለዚህ አንሶ ነው ወይ? ምንድነው ቸግሩ? የት ላይ ነው እጥረቱ?

     እናም አንዱ "ምርምሬ" ውጤት ቬንቲሌተር የተባለውን መሳሪያ በምዕራብ ካሉ አገራት ሁሉ የአሜሪካ ሴቶች በብዛት ይጠቀሙበታል፤ ከእነዚህም ውስጥ በርከት የሚሉቱ በእድሜ የገፉ፣ ባል የሞተባቸው፣ በሕመም የአልጋ ቁራኛ ቢሆኑም የወሲብ ስሜታቸው ያልበረደ ወዘተ አይነት ናቸው" ሲል፤ ሌላው ጥናት ደግሞ "የለም ቬንቲሌተርና ሌላም ወሲብ የሚያነሳሳና እርካታ የሚሰጥ መሳሪያ የሚጠቀሙት በርከት ያሉ ፍቅረኛ ያላቸው ሴቶችም ጭምር ናቸው ይበልጥ እርካታ ለማግኘት ወይም ፍቅረኛ ተብዬው ሊሰጥ ያልቻለውን እርካታ ለማግኘት ይጠቀሙበታል" ሲል አሳረገ።

     ሁሉ ነገር "ተከድኖ ይብሰል" ስለሆነ እኛ ዘንድ የአገራችን ሴቶች "ደስታን በመሻት መብታቸው" እርካታን ያግኙ አያግኙ ለማወቅ የተጠበበ ሳይንሳዊ ምርምር ስለመኖሩ አላውቅም። ይሁንና አስናቀች ወርቁ የርካታ ማግኘት አለማግኘት ነገር ለእኛም አገር ወይዛዝርት ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ባንጸባረቀችበት አንድ ዜማዋ "ሰውማ መች ጠፋ አመል የሚከላ/ አይገኝም እንጂ ጠረንና ገላ" እንዳለች ትክዝ ይለኛል።

     የኛ ዘመኗ በዛወርቅ አስፋውም ይህንኑ ስታስረግጥ "ምን ወታደር ቢሆን አልሞ ሰታሪ/ ምን ነጋዴ ቢሆን ገንዘብ አበዳሪ/ ለፍቅር ጨዋታ አይበልጡም ካዝማሪ" ብላ በዚያ ወርቃማ ድምፅዋ አሳብዳናለች። መሬት ይቅለለውና ጥላሁን ገሠሠን እንደምን ብዙ የአገራችን ሴቶች አቅላቸውን ሳቱለት? እሱም "ሆድ ይፍጀው" እንዳለ አለፈ፤ ሴቶቹም "ተከድኖ ይብሰል" እንዳሉ አረው ያልፋሉ ትዝታቸውን፣ ታሪካቸውን፣ ገድላቸውን ሳያወሱን! ለትውልድ ትውፊት እንዳይሆን እንደነፈጉን!

ማሳረጊያ

     በፍቅር ይታወቃል ባልነው ፈረንሳይ እንጀመርን በፈረንሳይ እናጠናቀው! Leon Uris በጻፈው Armageddon

መጽሐፍ ላይ ናዚ ጀርመንን ለመውጋት ትብብር አድርገው የነበሩት የአሜሪካ፣ የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ እንዲሁም ሶቭዬት ህብረት ምስራቅ ጀርመንን በርሊን ላይ ግምብ አጥሮ  ለብቻው በሶሺያሊዝም ካባ እስኪጠቀልል ድረስ ወዳጅ ሆነው ጀርመን ላይ ወታደሮቻቸውን አስፍረው የነበረበትን ሁኔታ ይስልልናል።


   ለጥቆም የወታደሮቹን ጭውውት በተለይም የፈረንሳዩ ወታደር ለአሜሪካኑ ወታደር ያለውን ንቀት እንደሚከተለው ያስቀምጥልናል።

    ፈረንሳዩ ወታደር አሜሪካኑን "አለምን ሳታውቁ የአለም ልዕለ ኃያል ሆናችሁ" ካለው በኋላም በፍቅር ጨዋታም ልፍስፍስ ናችሁ፤ የጀርመን ሴቶች ገና መኝታ ክፍል ገብታችሁ ኮፊያችሁን ሰቅላችሁ አልጋ ላይ በወጣችሁበት ፍጥነት ኮፍያችሁን መልሳችሁ አጥልቃችሁ ተመልሳችሁ የምትወጡበትን ፍጥነት “Wham! Bam! Thank you Madam! በሚል ፌዝ ማላጋጫ አድርገውታል" ይለዋል ካላዛባሁት በጣም የዛሬ ስንትና ስንት ዓመት ያነበብሁትን መጽሐፍ።



    ለማንኛውም ስለ ፍቅር በፍቅር ማናቸውም መንገድ ደስታን መሻት መብታችን ነው! ጨረስኩ ጉራማይሌይን!                  

No comments:

Post a Comment